✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞ ❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖ ❖ የካቲት 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት + " በዓለ ስምዖን " + =>ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን ጌታ በተወለደ በ40 ቀኑ ራሱ የሠራውን ሕግ ይፈፅም ዘንድ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቷል:: እንደ ሥርዓቱም እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምና አገልጋዩዋ ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ የርግብ ግልገሎችና ዋኖስ አቅርበዋል:: +ለ284 ዓመታት የአዳኙን (የመሢሁን) መምጣት ይጠብቅ የነበረው አረጋዊው ስምዖን በዚህች ዕለት ስላየውና ስለታቀፈው ዕለቱ በዓለ ስምዖን ይባላል:: (ሉቃ. 2:22) ከዘጠኙ የጌታ ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው:: +ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- +ከዓለም ፍጥረት በ5,200 ዓመታት (ማለትም ከክርስቶስ ልደት 300 ዓመታት በፊት) በጥሊሞስ የሚሉት ንጉሥ በግሪክ ነገሠ:: +በጊዜውም በኃይለኝነቱ ሁሉን አስገብሮት ነበርና "ዓለሙን እንደ ሰም አቅልጬ: እንደ ገል ቀጥቅጬ ገዛሁት:: ምን የቀረኝ ነገር አለ?" ሲል ተናገረ:: ባሮቹም "አንድ ነገር ቀርቶሃል:: በምድረ እሥራኤል ጥበብን የተሞሉ 46 መጻሕፍት አሉ:: እነርሱን አስተርጉም" አሉት:: +ያን ጊዜ እሥራኤላውያንን አስገብሯቸው ነበርና 46ቱን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ከ72 ምሑራን (ተርጉዋሚዎች) ጋር እንዲያመጡለት አዛዦቹን ላከ:: እነርሱም 46ቱን መጻሕፍተ ብሉይ ኪዳን ከ72 ምሑራን ጋር አመጡለት:: +አይሁድ ክፋተኞች መሆናቸውን ሰምቷልና 36 ድንኩዋን አዘጋጅቶ: ጥንድ ጥንድ ሆነው እንዲሠሩ: ሲተረጉሙ እንዳይመካከሩ 36 ጠባቂዎችን ሾመባቸው:: ይህ ነገር ለጊዜው ከንጉሡ ቢመስልም ጥበቡ ግን ከእግዚአብሔር ነው:: +ምንያቱም በጊዜ ሒደት መጻሕፍተ ብሉያት በአደጋ እንደሚጠፉ ያውቃልና ሳይበረዙ ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ለእኛ እንዲደርሱ ነው:: ስለዚህም ከክርስቶስ ልደት 284 ዓመት በፊት 46ቱም ሁሉም መጻሕፍት (ብሉያት) ከእብራይስጥ ወደ ጽርዕ ልሳን በ70ው ሊቃናት አማካኝነት ተተረጐሙ:: (በእርግጥ ከዚያ አስቀድሞ መጻሕፍት (ብሉያት) ወደ ሃገራችን መምጣቸውና ወደ ግዕዝ ልሳን መተርጐማቸውን ሳንዘነጋ ማለት ነው) +ወደ ዋናው ጉዳያችን ስንመለስ ከ70ው ሊቃናት መካከል በእድሜው አረጋዊ የሆነ (እንደ ትውፊቱ ከሆነ 216 ዓመት የሆነው) ስምዖን የሚሉት ምሑረ ኦሪት ነበር:: በፈቃደ እግዚአብሔር ለእርሱ መጽሐፈ ትንቢተ ኢሳይያስ ደርሶት እየተረጐመ ምዕራፍ 7 ላይ ደረሰ:: +ቁጥር 7 ላይ ሲደርስ ግን "ናሁ ድንግል ትጸንስ: ወትወልድ ወልደ" የሚል አይቶ "አሁን እንኳን የአሕዛብ ንጉሥ የእሥራኤልስ ቢሆን ድንግል በድንግልና ጸንሳ ትወልዳለች ብለው እንዴት ያምነኛል!" ሲል አሰበ:: "በዚያውስ ላይ ኢሳይያስ በምናሴ የተገደለው ስለዚህ አይደል!" ብሎ ቃሉን ሊለውጠው ወሰነ:: +አመሻሽ ላይም ድንግል የሚለውን ወለት-ሴት ልጅ ብሎ ቀየረው:: እርሱ ሲያንቀላፋ ቅዱስ መልአክ ወርዶ ድንግል ብሎ አስተካከለው:: ከእንቅልፉ ሲነቃ ግራ ተጋብቶ እንደ ገና ፍቆ ቀየረው:: +አሁንም መልአኩ ድንግል ሲል ቀየረበት:: 3 ጊዜ እንዲህ ከሆነ በኋላ ግን መልአኩ ተገልጦ ገሰጸው:: በዚያውም ላይ "ይህችን ድንግልና መሲሑን ልጇን ሳታየውና ሳትታቀፈው ሞትን አታይም" ብሎት ተሰወረው:: አረጋዊ ስምዖን ከዚያች ዕለት በኋላ የመድኅን ክርስቶስን መምጣት ሲጠብቅ ለ284 ዓመታት የአልጋ ቁራኛ ሁኖ ኖረ:: አካሉም አለቀ:: +ለስም አጠራሩ ስግደት የሚገባው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው በሆነበት በዚያ ሰሞን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ:: +ሕግን የሠራ ጌታ እርሱ ፈጻሜ ሕግ ይባል ዘንድ የርግብ ግልገሎችን (ዋኖሶችን) ይዘው በተወለደ በ40 ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ አስገቡት:: በዚህች ቀንም ቅዱስ መልአክ መጥቶ ቅዱስ ስምዖንን ከአልጋው ቀሰቀሰው:: ተስፋ የሚያደርገው አዳኙ (መሲሑ) እንደ መጣም ነገረው:: +ይህን ጊዜ አረጋዊው አካሉ ታድሶ እንደ 30 ዓመት ወጣት እመር ብሎ ከአልጋው ተነሳ:: እንደ በቅሎ እየሠገረም ወደ መቅደስ ወጣ:: በዚያ መሲሑን (ፈጣሪውን) ሲመለከት እንደ እንቦሳ ዘለለ:: ቀረብ ብሎም ሕጻን ጌታን ከድንግል እናቱ እጅ ተቀበለው:: +ከደስታው ብዛት የተነሳም "ይእዜ ትስዕሮ ለገብርከ: በሰላም እግዚኦ በከመ አዘዝከ-አቤቱ ባሪያህን እንደ ቃልህ በሰላም አሰናብተው" ሲል ጸለየ:: ትንቢትንም ተናገረ:: በዚያችው ዕለትም ዐርፎ ተቀበረ:: +"+ ሐና ነቢይት +"+ +ዳግመኛ በዚህች ቀን አረጋዊቷን ነቢይት ቅድስት ሐናን እናስባለን:: ይህች ቅድስት ትውልዷ ከነገደ አሴር ሲሆን አባቷ ፋኑኤል ይባላል:: በትውፊት ትምሕርት ሐና የተዳረችው በልጅነቷ (በ12 /15/ ዓመቷ) ነው:: ለ7 ዓመታት ከልጅነት ባሏ ጋር ኖራ ዕድሜዋ 19 (22) ሲደርስ ሞተባት:: +እንደ እሥራኤል ልማድ ሌላ እንድታገባ ብትጠየቅም እንቢ ብላ መበለት ሆነች:: ራሷንም ለእግዚአብሔር አሳልፋ ሰጠች:: በቤተ መቅደስም ለ84 ዓመታት ለፈጣሪዋ ተገዛች:: ፈጽማ ትጸልይና ትጾም ነበርና በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ውጪውን አልተመለከተችም:: +ለእርሷ 103 (106) ዓመት ሲሆን መድኃኒታችን ተወለደ:: በዚህች ቀን ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ተመልክታም ጌታን ባረከች:: ደስ እያላትም ትንቢትን ተናገረች:: ወደ ቤቷ ገብታም ነፍሷን ሰጠች:: (ሉቃ. 2:36-38) ❖ቸሩ መድኃኒታችን ተርፎ ከሚቀረው ዘመን ዕድሜ ለንስሃ: ዘመን ለፍሥሐ አይንሳን:: ከቅዱሳኑ በረከትም አይለየን:: ✞የካቲት 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅዱስ ስምዖን አረጋዊ 2.ቅድስት ሐና ነቢይት (የፋኑኤል ልጅ) 3.ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ እግዝእት 4.አባ ኤልያስ ገዳማዊ (በትህትና ያጌጠ ቅዱስ ሰው) ❖አረጋዊ ስምዖንን ከድካም አልጋ ያነሳ አምላከ ቅዱሳን እኛንም ድካመ ነፍስን ከሚያመጣ የበደል ምኝታ በቸርነቱ ያንሳን:: ++"+ እንደ ሕጉ ልማድ ያደርጉለት ዘንድ ሕጻኑን ጌታ ኢየሱስን በአስገቡት ጊዜ እርሱ ደግሞ ተቀብሎ አቀፈው:: እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ:- ጌታ ሆይ! አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ:: ዓይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና:: ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን: ለሕዝብሕም ለእስራኤል ክብር ነው:: ዮሴፍና እናቱም ስለ እርሱ በተባለው ነገር ይደነቁ ነበር:: +"+ (ሉቃ. 2:27) ✞ ✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞ ✞ 1.4K views17:39