Get Mystery Box with random crypto!

ዝክረ ቅዱሳን ማኅበረ ቅዱስ ዳዊት - ዘብሔረ ጎንደር (ዲ/ዮርዳኖስ አበበ): ††† እንኳን ለታላ | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

ዝክረ ቅዱሳን ማኅበረ ቅዱስ ዳዊት - ዘብሔረ ጎንደር (ዲ/ዮርዳኖስ አበበ):
††† እንኳን ለታላቁ ገዳማዊ አባ ጳውሊ እና ለጻድቁ አባ ለንጊኖስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ታላቁ ቅዱስ ጳውሊ †††

††† በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ "ታላቁ /ዐቢይ/ THE GREAT" የሚል ስም የሚሰጣቸው አባቶች የተለዩ ናቸው። አንድም እጅግ ብዙ ትሩፋቶችን የሠሩ ናቸው። በሌላ በኩል ደግሞ በተመሳሳይ ስም ከሚጠሩ ሌሎች ቅዱሳን እንለይበታለን።

ገዳማዊ ሕይወት ጥንቱ ብሉይ ኪዳን ነው። በቀዳሚነትም በደብር ቅዱስ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ደቂቀ ሴት እንደ ጀመሩት ይታመናል። ሕይወቱ በጐላ በተረዳ መንገድ የታየው ግን በታላቁ ጻድቅ ሄኖክ ከዚያም በቅዱሱ ካህን መልከ ጼዴቅ አማካኝነት ነው።

ቀጥሎም እነ ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ እነ ኤልሳዕ ደቀ መዝሙሩ ኑረውበታል። በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ሙሉ ሕይወቱን በገዳም (በበርሃ) ያሳለፈው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቅድሚያውን ይይዛል።

ለስም አጠራሩ ስግደት ይሁንና መድኃኒታችን ክርስቶስ በገዳመ ቆረንቶስ ለአርባ ቀናት በትሕርምት ኑሮ ገዳማዊ ሕይወትን ቀድሷል፤ አስተምሯል። በዘመነ ስብከቱም ያድርባት የነበረችው የደብረ ዘይቷ በዓቱ (ኤሌዎን ዋሻ) በራሷ ለዚህ ሕይወት ትልቅ ማሳያ ናት።

ከጌታ ዕርገት በኋላም ክርስቲያኖቹ የዓለም ሁካታ ሲሰለቻቸው አንድም በንጹሕና በተሸከፈ ልቡና ለፈጣሪያቸው መገዛትን ሲሹ ከከተማ ወጣ እያሉ ይኖሩ እንደ ነበር የታሪክ መዛግብት ያሳያሉ። አኗኗራቸውም በቡድንም በነጠላም ሊሆን ይችላል። ዋናው ነገር ግን በጾምና በጸሎት መትጋታቸው ነው። ይህም ሲያያዝ እስከ ሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ደረሰ። በዚህ ዘመን ግን አባ ጳውሊ የሚባል ንጹሕ ክርስቲያን ይህንን ሕይወት ወደ ሌላ ደረጃ ከፍ አደረገው። ለሰማንያ ዓመታት ሰው ሳያይ ተጋድሎ "የባሕታውያን አባት" ተባለ። ደንብ ያለው ተባሕትዎም ጀመረ።

ይህ ከሆነ ከሃያ ዓመታት በኋላ ደግሞ አባ እንጦንስ የሚባሉ ደግ ክርስቲያን ይህንን ገዳማዊ ሕይወት በሌላ መንገድ አጣፈጡት። በቅዱስ ሚካኤል አመንኳሽነት ገዳማዊ ሕይወት በምንኩስና ተቃኘ። ስለዚህም አባ እንጦንስ የመነኮሳት አባት ተባሉ።

እርሳቸውም ሕይወቱን ለማስፋፋት ከተለያዩ አሕጉር ደቀ መዛሙርትን እየተቀበሉ አመንኩሰዋል። ቅዱሳን የአባ እንጦንስ ልጆችም ወደየ ሃገራቸው ተመልሰው ሕይወቱን በተግባር አሳይተው ገዳማዊነትን አስፋፍተዋል።

አንድ ቀን ቅዱስ እንጦንስ (የመነኮሳት ሁሉ አባት) እንዲህ ሲል አሰበ። "በውኑ በበርሃ ለበርካታ ዘመናት በመኖር ከእኔ የሚቀድም (የሚበልጥ) ሰው ይኖር ይሆን?"
ይህንን ሃሳቡን ገና ሳይጨርሰው ቅዱስ ሚካኤል ወደ እርሱ ዘንድ ደረሰ።

"እንጦንስ ሆይ! ከእኔ የሚቀድም የበርሃ ሰው ይኖር ይሆን ብለህ አስበሃል። በእርግጥም ከአንተ ሃያ ዓመታትን ቀድሞ ወደ በርሃ የገባ፣ በቅድስናው ፈጣሪውን ያስደሰተ፣ ዓለም ከነ ክብሯ የእግሩን መረገጫ ያህል እንኳ የማትመጥነው በጸሎቱና በምልጇው ዓለም የምትጠበቅለት ሞገስን የተሞላ አንድ ሰው በበርሃ ስላለ ሒድና ተመልከተው።" ብሎት ተሠወረው።

ቅዱስ እንጦንስም ከሰማው ነገር የተነሳ እየተደነቀ ተነሳ። እርሱ ካለበት በርሃ በራቀ መንገድም ለቀናት ተጉዞ አንድ በዓት (ዋሻ) በር ላይ ደረሰ። በበሩ አካባቢ የሰውና የአራዊት ኮቴ ተመልክቶ በሩን ጸፋ (ቆፈቆፈ)። በውስጥ ያለው አረጋዊ ሰው ግን ትልቅ ድንጋይ ገልብጦ በሩን አጠበቀው። ለሰማንያ ዓመታት ሰውን አይቶ አያውቅምና ሰይጣን ሊያታልለኝ መጥቷል ብሎ አስቧል። ቅዱስ እንጦንስ ግን "ኃሠሥኩ እርከብ ጐድጐድኩ ይትረኃው ሊተ - ሽቻለሁና ላግኝ፤ ደጅ መትቻለሁና ይከፈትልኝ።" ሲል አሰምቶ ተናገረ።

ቅዱሱ ገዳማዊም ሰው መሆኑን ሲያውቅ በሩን ከፈተለትና ወደ ዋሻው አስገባው። መንፈሳዊ ሰላምታንም ተለዋወጡ። ሲመሽም ቅዱስ እንጦንስ ሽማግሌውን ገዳማዊ "ስምህ ማን ነው?" ቢለው "ስሜን ካላወክ ለምን መጣህ?" ሲል መለሰለት።

ያን ጊዜ ቅዱስ እንጦንስ ቀና ብሎ ሰማይን ሲመለከት ምሥጢር ተገለጠለትና "ቅዱስ ጳውሊ ሆይ! ከአንተ ጋር ያገናኘኝ ፈጣሪ ይክበር፤ ይመስገን።" ሲል ፈጣሪውን ባረከ። ቅዱስ ጳውሊም መልሶ (በጸጋ አውቆት) "አባ እንጦንስ ሆይ! እንኳን ደህና መጣህ።" አለው። ሁለቱም ደስ ብሏቸው ፈጣሪያቸውን እያመሰገኑ ተጨዋወቱ።

ቤተ ክርስቲያን ለሁሉም ዓይነት የቅድስና ሕይወት የመጀመሪያ የምትላቸው አላት። ለምሳሌ፦
የመጀመሪያው ሐዋርያ ቅዱስ እንድርያስ፣
የመጀመሪያው ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ፣
የመጀመሪያው ባሕታዊ (ገዳማዊ) ቅዱስ ጳውሊ እና የመጀመሪያው መነኮስ ቅዱስ እንጦንስን ማንሳት እንችላለን።

ቅዱስ ጳውሊ የተወለደው በሰሜናዊ ግብጽ በእስክንድርያ ከተማ ሲሆን ዘመኑም ሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ነው። ወላጆቹ ባለጸጐች ነበሩ። ቅዱሱንና ታላቅ ወንድሙን አባ ጴጥሮስን ወልደዋል። ሁለቱ ክርስቲያን ወንድማማቾች ገና ወጣት ሳሉ ወላጆቻቸው ሞቱባቸው። ሃዘናቸውን ፈጽመው ሃብት ሲካፈሉ ግን መስማማት አልቻሉም።

ምክንያቱ ደግሞ ትልቁ ጴጥሮስ ደህና ደህናውን እቃ ወስዶ መናኛ መናኛውን ለትንሹ ለጳውሎስ (ጳውሊ) መስጠቱ ነበር። ስለዚህ ነገር ተካሰው ወደ ፍርድ ቤት ሲሔዱ ግን መንገድ ላይ አንድ ባለጸጋ ሙቶ ደረሱ።

ቆመው ሳሉም ቅዱስ መልአክ ሰው መስሎ ጳውሊን "ይህ ሰው ባለጸጋ ነው። በገንዘቡ የሰጠውን ፈጣሪ ሲበድልበት ኑሮ እነሆ ተሸኘ። በሰማይም አስጨናቂ ፍርድ ይጠብቀዋል።" ሲል ነገረው።

በዚያች ቅጽበት የወጣቱ ጳውሊ ሐሳብ ተለወጠ። ወደ ወንድሙ ተመልሶ "ወንድሜ ሆይ! ሁሉ ንብረት ያንተ ይሁን።" ብሎት ከአካባቢው ጠፋ። በመቃብር ሥፍራ ለሦስት ቀናት ያለ ምግብ ጸልዮ የእግዚአብሔር መልአክ ሰው ወደ ማይደርስበት በርሃ ወሰደው።

በዚያም ምንጭ ፈለቀችለት። እየጾመ ይጸልይ ይሰግድ ገባ። ሁሌ ማታ ግማሽ ሕብስት ከሰማይ እየወረደለት ቅዳሜና እሑድ መላእክት እያቆረቡት ለሰማንያ ዓመታት ኖረ። (አንዳንድ ምንጮች ግን ለዘጠና ዓመታት ይላሉ።) ከቅዱስ እንጦንስ ጋር የተገናኙትም ከዚህ በኋላ ነው።

ከቅዱስ እንጦንስ ጋር በነበራቸው የሁለት ቀናት ቆይታም ቅዱስ ጳውሊ ብዙ ትንቢቶችን ተናግሯል። በዚህች ቀን ሲያርፍም መቃብሩን አናብስቱ ቆፍረዋል። ቅዱስ እንጦንስም በክብር ቀብሮታል። ለሰማንያ ዓመታት የለበሳት የዘንባባ ልብሱም ሙት አስነስታለች።

††† ጻድቅ፣ ቡሩክ፣ ቀዳሚው ገዳማዊ፣ መላእክትን የመሰለና የባሕታውያን ሁሉ አባት ለተባለ ለቅዱስ ጳውሊ ክብር ይገባል!

††† አባ ለንጊኖስ †††

††† ጻድቁ ከኪልቅያ እስከ ሶርያ ከሶርያ እስከ ግብጽ ድረስ በተጋድሎ የተጓዙ አባት ናቸው። በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽም የደብረ ዝጋግ (ግብጽ፤ እስክንድርያ) አበ ምኔት ሆነው አገልግለዋል።

ሙታንን አስነስተው ሃይማኖታቸውን ጠብቀው ብዙ ተአምራትን ሠርተው በዚህች ቀን ዐርፈዋል። ከድንቅ ነገራቸው ሰይጣን የእርሳቸውን የምንኩስና ቆብ ዐይቶ ደንግጦ መሸሹን እንጠቅሳለን።
"ኀበ ኢኀሎከ ሶበ ቆብዓከ ርዕየ
ሰይጣን ተኃፊሮ እፎኑመ ጐየ።" እንዲል።
(አርኬ)

††† አምላክ በበረከታቸው ይባርከን።