እሷ (ፉአድ ሙና) . ይፈሳል እንባዋ ፣ ትማፀነዋለች ሀዘን ተቀልፃ፣ "ወዴት ነው ‘ምትሄደው?" ትጠይቀዋለች ድንጋጤ ለብሳ። አይመልስም እርሱ ፣ የያዘው ይዞታል ፣ ቃል አይወጣም ከአፉ፣ "ለማን ነው ‘ምትተወን?" አታውራ ቢለው ነው ለመልስ መስነፉ። በአስፈሪ በረሀ ፣ ጡት ያልጣለን ህፃን የሚያስተው ጭካኔ፣ ታሰላስላለች ፣ ከየት አመጣ ወኔ? "አላህ ነው ያዘዘህ?" አይኖቿ ዋተቱ ምላሹን ፍለጋ፣ "አዎ" ሲል መለሰ ፣ ልቧ ተረጋጋ! "እርሱማ ከሆነ ጥሎ አይጥለንም!" ስትል ተናገረች በኢማን ተውባ፣ የአላህ እርዳታ እንደሚደርስላት በፅኑ አስባ። . ትቷቸው ሲመለስ ልቡን ሊያረጋጋ ፣ ጌታውን ለመነ እጆቹን ዘርግቶ፣ በልጁ ስቅይት ፣ በሚስቱ ተማፅኖ አንጀቱ ተበልቶ። "ጌታችን ሆይ! ከቤትህ አቅራቢያ ፣ አንተን ይገዙ ዘንድ፣ አዝመራ ከሌለው ፣ ከሸለቆው ንዳድ፣ ትዕዛዝህን ብዬ ፣ ዘሮቼን አስቀመጥኩ፣ ፍላጎቴን ገደብኩ ፣ መሻትህን ፈፀምኩ። ጌታችን ሆይ! የሰዎችህን ልብ ፣ አስናፍቅ ወደነርሱ፣ ከፍሬህ ስጣቸው ፣ ያመስግኑህ ለሱ። ጌታችን ሆይ! ድብቁን ታውቃለህ ፣ የምንሰውረውን፣ ተለየሁ ከእነርሱ ፣ ጌታዬ አደራህን!" . ከሄደ በኋላ ስንቋም ተራገፈ ፣ ውሀም ለአመል ጠፋ፣ ጥሙ ጠበሳቸው ፣ ረሀቡም ከፋ። ስትሮጥ ከጋራው ላይ ፣ ሶፋና መርዋን ስትመላለሰው፣ ቃሏን አሟላላት ፣ ቃሉን የማይጥሰው። በመልዓኩ ክንፍ ፣ ሲቆፈር አፈሩ፣ "ዙሚ ዙሚ" አሰኛት ፣ ቀናላት ነገሩ። "ጥሎ አይጥለንም!" ተወዶ እምነቷ፣ ለዓለም ፈውስ ሆነ ፣ ሀጀር ትሩፋቷ። . @Fuadmu @Fuadmu 4.1K views18:00