Get Mystery Box with random crypto!

፨ሥዕለ ፍልሰታ ለማርያም፨ | ኦርቶዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት: Ethio Icons

፨ሥዕለ ፍልሰታ ለማርያም፨
በኃይለማርያም ሽመልስ /ሠዓሊና በቅዱሳት ሥዕላት ዙርያ አጥኚ/

ውድ የዚህ ድረ ገጽ ተከታታዮች እንኳን ለደስተኛይቱ ክብርት ስለሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም የሥጋዋ ፍለሰት በሰላም አደረሳችሁ፡፡ ለዛሬ ከቤተ ክርስቲያናችን እንደ ጠፈር ሰፊና እንደ ውቅያኖስ ጥልቅ ከሆነው የእመቤታቸን ነገረ ሕይወቷንና ተአምራቷን ከሚገልጡት ሥዕሎች መካከል ተወዳጅ የሆነውን የፍልሰታዋ ሥዕልን አጭር መግለጫ ከአሣሣሉ ጋር አቅርቤያለሁ፡፡ መልካም ንባብ

የእመቤታችን ፍቅሯ ጠዓሟ እና አማላጅነቷ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማታያስ እና ሌሎች ብፁዓን ጳጳሳት አባቶቻችንና ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ይኑር፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሥዕሎች ምንጫቸው መጽሐፍ ቅዱስና አዋልድ መጻሕፍት ሲሆን፤ በእነዚህ መጻሕፍት ውስጥ የተገለጠው እውነትም በጊዜ እና በቦታ ሳይወሰን ቅዱሳት ሥዕሎች ይሣላሉ፡፡ ከእነዚህ ሥዕሎች መካከልም የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የፍልሰተ ሥጋዋ ሥዕል አንዱ ነው፡፡

ለዚህ ሥዕል መነሻ ታሪክ ደግሞ በመጽሐፍ ቅዱስ በትንቢት ተነግሮ በኋላ ትንቢቱ ሲፈጸም የተከሰተውና በትውፊት የተቀበልነው የአምላክ እናት የቅዱስ ሥጋዋ ከዚህች ምድር ወደ ሰማያት ማረግ ነው፡፡ ታሪኩም እመቤታችን ለሰዎች ልጆች ስትል በጥር 21 ቀን ከዚህ ዓለም ድካም አርፈች፡፡ ክፉዎች አይሁድም ሥጋዋን ሊያቃጥሉ ሽተው ነበር፡፡ ይህ እንዳይሆን ጌታችን ቅዱስ ሥጋዋን ወስዶ ገነት አኖረው፡፡

ሐዋርያትም ሱባኤ ቢይዙ ዳግም ቅዱስ ሥጋዋን ከገነት አምጥቶ ሰጣቸው በሰኔ 14 ቀንም ቀበሯት፤ በሰኔ 16 ቀንም እንደ ልጇ በሦስተኛው ቀን ተነስታ ያረገችበት ተአምራታዊ ተነሥታለች፡፡

በዚህን ጊዜም ቅዱስ ቶማስ ከሐዋርያት ጋር በአገልግሎት ምክንያት አልነበረም፤ ነገር ግን ደመና ጠቅሶ ሲሔድ እመቤታችን በብዙ መላእክት ተከባ በምስጋና ስታርግ ያገኛታል፡፡ እርሱም የጌታን ትንሣኤ (በመጀመሪያው መገለጥ) አመለጠኝ አሁንም የእመቤታችን ትንሣኤ አመለጠኝ በማለት አዘነ፡፡ እመቤታችንም እነርሱ ትንሣኤን አላዩም አንተ እንጂ ብላ ለምልክት እንዲሆን ሰበኗን ሰጠችው፡፡

ቅዱስ ቶማስም ወደ ሐዋርያት ሔዶ ስለ እመቤታችን ቢጠይቃቸው እረፍቷ በጥር ቀብሯ ደግሞ በነሐሴ ቢሉት፤ እንዴት ይህ ሊሆን ይችላል በማለት ቅዱሰ ቶማስ ጠየቃቸው በዚህም ወቅት ቅዱሳን ሐዋርያትም ወደ መቃብሯ ሲሔዱ ቅዱስ አካሏን አጡት፡፡ በዚህን ጊዜ ቢደነግጡ ቅዱስ ቶማስ ሰበኗን አሳይቶ ወደ ሰማይ ማረጓን ነገራቸው፡፡ እነርሱም ሱባኤው ቢገቡ እመቤታችንን ተገልጣላቸዋለች፡፡

እኛም ኦርቶዶክሳውያን ይህንን ታሪክ በማሰብ በፍቅርና አንድነት የፍልሰታ ጾምን በጾም በነሐሴ 16 የፍልሰታ በዓሏን እናከብራለን፡፡ ከስርም የቤተ ክርስቲያን ሠዓሊያን በተለያዩ ዘመናት እንዴት የፍለስታ ሥዕሏን እንደሣሉ እንመለከታለን፡፡

የፍልሰታ ለማርያም ሥዕል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን

የፍልሰታ ሥዕል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከእመቤታችን ሥዕሎች መካከል አንዱ ሲሆን፤ በተለይ ከ17ኛው መ.ክ.ዘ. ወዲህ ይህ ሥዕል በሚዘጋጁ የብራና መጻሐፍት ላይ፣ የግድግዳ እና የገበታ ላይ መታየት ጀመረ፡፡ የፍልሰታ ለማርያም ሥዕልም በተለያየ መልኩ በየዘመናቱ እየተሣለ የተለያዩ ገጸ ባሕርያትን በማካተት ወዳለንበት ዘመን ደርሷል፡፡
የፍልሰታ ለማርያም ሲሣልም በተለያየ መንገድ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የተሣለ ሲሆን ከእነርሱ መካከል ከሥር በዝርዝር ቀርበዋል፡፡

1ኛ ጨረቃን የረገጠችው እመቤት

እመቤታችን ጨረቃን በእግሮቿ ረግጣ፣ በደመና ተጭና እና በቅዱሳን መላእክት ተከባ ስታረግ ይሣላል፡፡ ከዮሐ ራእይ 12 ላይ ያለችውን ፀሐይ የታቀፈች ጨረቃም የእግሮቿ መረገጫ የሆነችውን ንግሥተ ሰማይ ጋር ይገናዘባል፡፡

2ኛ. ለሐዋርያው ቶማስ ሰበኗን ስትሰጠው

ጨረቃዋን ረግጣ ከመታየት በተጨማሪም ለቅዱስ ቶማስ ሰበኗን ስትሰጠው አሊያም ቅዱስ ቶማስ ጋር ስትነጋገር የሚያሳየው ታሪክም በፍልሰታ ሥዕል ላይ ይታያል፡፡ ሐዋርያው ቶማስም በደመና ላይ ሆኖ ሰበኗን በመቀበል ላይ እያለ ወይም በስፋት ባይታይም ስታረግ እየተመለከት ይሣላል፡፡ ጨረቃ ሳትረግጥና በመላእክት እየተመሰገነች ሰበኗን ስትሰጠው ተሥሎ ይገኛል፡፡

ቅዱስ ቶማስ ከእመቤታችን ሰበኗን ከመቀበል በተጨማሪ ሐዋርያትን ስለ እመቤታችን ሥጋ ሲጠይቃቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ሲቆፍር እና ሌሎቹ ሐዋርያት አጆቻቸውን በአግራሞት ፊታቸው ላይ አድርገው ተሥሎ በአንድ ላይ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ በመሐል ዘጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚታየው የፍልሰታ ለማርያም ሥዕል ነው፡፡

በዚህ የፍልሰታ ሥዕል ላይ የቅዱስ ቶማስ ሥዕል በተደጋጋሚ ተሥሎ ይታያል፡፡ ይህ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ሥዕሎች መለያ መገለጫዎቹ አንዱ የሆነውን አንድ ገጸ ባህርይ ከአንድ ጊዜ በላይ በአንድ የሥዕል ድርሰት ላይ መታየት ሲሆን፤ በሥዕሎቹ ላይ ይህ መታየቱ ደግሞ ቅዱሳት ሥዕላት በጊዜ እና ቦታ የማይወሰኑ በመሆናቸውና እንዲሁም ዓላማቸው በግልጽና በአጭር መልኩ ቋንቋ ሥነ መለኮታዊ እውነታን ማስረዳት በመሆኑ ነው፡፡

3ኛ ቅዱስ ጊዮርጊስ እመቤታችንን ሲማጸን

ቅዱስ ጊዮርጊስ እመቤታችንን ፍልሰቱን ከፍልሰታዋ እንድትደምረው ሲማጸን በፍልሰታዋ ሥዕል ላይ ተጨምሮ ይሣላል፡፡ ይህ ደግሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቅዱስ አጽሙ በነሐሴ 16 ቀን በታላቅ ደስታ ከፋርስ ወደ ልዳ የምትገኘው ቤተ ክርስቲያን መፍለሱን ያስታውሳል፡፡

በስንክሳር ላይም እንደተጠቀሰው እርሷን የሚወዱና በእርሱ ስም ለሚጸልዩ ለሚማጸኑ የድኅነት መንገድ እንዲሆናቸው የእርሱን ሥዕል ከእርሷ ሥዕል ጋር አብረው ይሥላሉ።

ይህንን በሚገልጽ መልኩ የፍልሰታ ለማርያም ሥዕል የተሣለ ሥዕል በመሐል ዘጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ ሰማዕቱ የክብር ልብሶ ‹‹ምሰለ ፍለሰትኪ ደምርኒ እሙ›› ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት፡፡