ወዳጄ ሆይ ያለፈ ነገር አይቀዪርም ፣ ላወቀበት ሰው ግን ያለፈው ለወደፊቱ የራሱ የሆነ ትምህርት አለው ፣ ካለፈው ነገርህ ተማር እንጅ በፍፁም አታማርር ፣ ማማረር ነገህን በጎ አያደርገውም የሰዎች ሃሳብ የአንተን ማንነትአይገልፅም ፣ማንነትህ አንተ ውስጥ ነው ያለው ፣ መልካም አድርግ ሌላውን እርሳው የሁሉም ሰው የህይወት መንገድ (ጉዞ) ይለያያል ፣ጊዜው በደረሰ ሰው ሁኔታ አትቅና ለሁሉም ጊዜ አለው ። በራስህ ላይ አተኩር ፣ ያለህ ነገር በቂ ነው ።በሰዎች ደስታ ደስ ይበልህ ፣ ክፉ አትመኝ ፣ በሃዘናቸውም አብረህ እዘን ሲያዝኑ አትደሰት ፣ ሰው ከሆንክ የሰው ነገር ይሰማህ ፣ይህ ማለት ግን ተንኮል እየሰሩ ከሚደሰቱ ሰዎች ተደሰት ማለት አይደለም ። ሰው እያስከፋ ብሎም እየገደለ የሚደሰት አለ ፣ አንተ ከተጎዳው ሰው ጋሁን ፣ አስተውል ። ጊዜ የማይፈውሰውና የማይቀይረው ነገር የለም አንተም ጊዜው ይቀይርህ ዘንድ ፍቀድለት ፣በተሰጠህ ጊዜ ለመልካም ነገር ሱሰኛ ሁን ። የስራ ጉዳይ ውስጥህ የሚችለውናየሚያምንበት ተሰጥኦ ምን አለህ ? ምን አይነት ስራ መስራት ትችላለህ ? አስተውል ጓደኛህን አትመልከት ፣ ትለያያላችሁ ፤አለማችን በትምህርት ብቻ ወይም በጥበባት ብቻ ወይም በተወሰኑ ዘርፎች አይደለችም እየኖረች ያለችው፣ በጣም ብዙ ነገሮች ናቸው እየደገፏት ያቆሟት ፤ አንተም ጥቂትም ብትሆን ያለህን ችሎታ አውጣው ፣ ፈልገው አጎልብተው ጀምረው ፣ "ምን ይሻለኛል ?" እያልክ አታመንታ ጊዜህ እንዳያልቅ ፣በእርግጥ ጊዜህ ሳይሆን አንተ ነህ የምታልቀው ። አስተውል ፣ መልካም ነገር ሁሉ ከፈጣሪ መጥፎ ነገር ሁሉ ደግሞ ከሰይጣን አይደለም ፣ ፈጣሪ መጥፎን ወደ መልካም የመቀዪር ብቃት አለው ። ሰይጣንም ያጠፋህ ዘንድ መልካም የሚመስል ነገር ሊያዘጋጅልህ ይችላል ፣አስተውል ። መልካም ማሰብና መልካም መሆን መልካም ነገር እንዲገጥምህ ማመቻቸት ነው ፣ መጥፎነት ከአንተ ይራቅ ፣ ለአንተም ሆነ ለሰዎች ጉዳት እንጅ ጥቅም የለውም ። የሰራኸውና የምትሰራው ነገር የሆነ ጊዜ ላይ ዞሮ ያገኝሃል ፣ መጥፎ ከሰራህ እንደስራህ ፣ መልካም ከሰራህም እንደዚያው ይገጥምሃል ። "ሰው የዘራውን ያጭዳል" የሚለውን አስታውስ ፣ ክፉ ነገር እየዘራህ መልካም ነገር አትጠብቅ ፣ራስህን አትሸውድ ። ጤፍ ዘርተህ ባቄላ አትጠብቅ ። ጤፍ የዘራ ገበሬ ጤፍ እንደሚያጭድ ሁሉ ፣ አንተም የዘራኸውን በእጥፍ ታጭዳለህ። ወዳጄ ሆይ! ለራስህ ስትል መልካም ሁን ፣ በጎውንም አስብ። ለራስ ማሰብ ማስተዋል እንጅ ራስ ወዳድነት አይደለም። ራሱን የማይወድ ሰው ሌላውን አይወድም ። አትፍረድ ፣ የመፍረድ ሃላፊነት በፍፁም የለህም ። ፍርድ የፈጣሪ ነው፣ ለመፍረድ እንከን አልባ መሆን ያስፈልጋል ፣ ፍጥረት ሁሉ ፍጥረት በመሆኑ ብቻ እንከን አለበት ፣ ጎደሎ አለበት ። የተሻለ ሀሳብ አለኝ ብለህ ካሰብክና ከቻልክ ምከር ካልሆነ ዝም በል ። ከጓደኛህ መልካም የሆነውን ነገሩን አውጣለት ፣አበረታታው፣እንደማይጠቅም አትንገረው ፣ ለሀዘኑ ሳይሆን ለደስታው ምክንያት ሁን ፣ ለስኬቱ እንጅ ለውድቀቱ መንስኤ አትሁን ። መልካም ጓደኛ ከፈጣሪ የሚሰጥ ጸጋ ነው ። መልካም ጓደኛ ፣ የማይቀና አሳቢና መካሪ ፣ ከእኔ ይልቅ ለአንተ የሚል ካለህ አንተ ተባርከሃል ታድለሃል ። ከሌለህ ደግሞ አንተ ራስህ መልካም በመሆን ጀምር ፣ ባህሪህንና ስራህን አይተው ይመጣሉ። ያለ መጠን ማሰብ ጭንቀትን ፣ ሀዘንን ያስከትላል ።ከአቅምህ ከምትችለው በላይ አታስብ ፣መመለስ በማትችለው ነገር ላይ አትወጠር ፣ የተመለሱ ነገሮችህ ላይ ትኩረት አታድርግ። አንዳንድ መልሶች በድጋሚ ጥያቄወች ሆነው እንደሚመጡ አትዘንጋ ። ባልገባን ሳይሆን በገባን ነገር ላይ እናተኩር ።ደግነት ዋጋ አያስከፍልም ነፃ ነው ፣ "ያስከፍላል"ብለህ ካሰብክም ምላሹ እጥፍ እንደሚሆንልህ አትዘንጋ። ደግ ሁኑ ፣ደግ ሆነው የተጎዱ የሉም ፣ ቢኖሩም ከጉዳታቸው ይልቅ በረከታቸው ሰላማቸው ልክ የለውም። ደስታህንና ሰላምህን የሆነ ሰው ወይም ነገር ላይ አታስቀምጥ ፣ ያ ነገር ወይም ሰው ከአጠገብህ ሲርቅ ወይም ሲጠፋ ደስታህም አብሮ ይጠፋል ። ደስታና ሰላም በአንተ ውስጥ ናቸው ። በራስህ በአፈጣጠርህ ደስ ይበልህ ፣ውለህ በመግባትህ ደስ ይበልህ ። በአለህ ትንሽ ነገር ደስ ይበልህ ። ለፍቅር ለመውደድ እንጅ ለጥላቻ ለዛቻ ለምቀኝነት ጊዜ አይኑርህ ። በመውደድ የተጠመደ ሰው ለመጥላት ጊዜ የለውም። እድሜህን በተመለከተ ፣ የፈጣሪ ፈቃድ ከሆነ ካለፈው ከተቃጠለው ጊዜህ ይልቅ ወደፊት የምትኖረው ብዙ ነው ። ዋናው ደግሞ የኖርክበት የእድሜ ብዛት ሳይሆን በኖርክበት ዘመን ያሳዪኸው መልካምነትና የሰራኸው ደግነት ነው። የምናማርረው የተሰጠንንና የሆነልንን ’ረስተን ፣ ያልጎደለን ነገር ላይ "ጎደለን" ብለን በጥያቄ ስለምንሞላ ነው ፣ ባለው ነገር አመስጋኝ የሆነ ይጨመርለታል ። በማማረር መባረክ የለም ። ሰላምና ጤና ፣ ከመልካም አስተሳሰብና በጎ ህሊና ጋር ምንጊዜም ከዘመንህ አይለዪ። ውብ ምሽት @EthioHumanity @EthioHumanity @EthioHumanityBot 1.3K viewsedited 17:50