2022-08-10 20:40:24
#ስለጾም
ጾም (ጦም) ማለት ሰውነትን ከመብል ከመጠጥና ከክፉ ስራ ከሐሜት ከመጥፎ ንግግርና ከኃጥያት ሁሉ መከልከል ማለት ነው ፡፡የጾም ጊዜ ራስን የማዋረድ የኃዘን የጸሎት የንስሐና የኑዛዜ ጊዜ እንደሆነ መጽሀፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡፡
- በአምላካችን ፊት ራሳችንን እናዋርድ ዘንድ፥ ከእርሱም የቀናውን መንገድ ለእኛና ለልጆቻችን ለንብረታችንም ሁሉ እንለምን ዘንድ በዚያ በአኅዋ ወንዝ አጠገብ ጾም አወጅሁ።(ዕዝ 8፡21)
- ይህንም ቃል በሰማሁ ጊዜ ተቀምጬ አለቀስሁ፥ አያሌ ቀንም አዝን ነበር በሰማይም አምላክ ፊት እጾምና እጸልይ ነበር፥(ነህ 1፡4)
- ማቅ ለብሼ በአመድም ላይ ሆኜ ስጾም እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ።(ዳን 9፡3)
የሚጾሙ ሰዎች በ 2 ይመደባሉ
- 1.የጾም ጊዜያቸው እስኪፈጸም ድረስ ያለምንም እህል ውሃ በባዶ ሆድ የሚጦሙ ሲሆን
- 2.ከስጋ ከቅቤ ከእንቁላልና ለስጋ ሃል ሰጪ ያልሆኑ ምግቦች እንዲሁም ከሚያሰክር መጠጥ በመከልከል እስከ ተወሰነ ሰዓት በባዶ ሆድ ቆይተው ሰዓታቸው ሲደርስ የሚመገቡ ናቸው፡፡
ያለ ምንም እህል ውሃ የሚጾሙ
- ሄደህ በሱሳ ያሉትን አይሁድ ሁሉ ሰብስብ፥ ለእኔም ጹሙ ሦስት ቀን ሌሊቱንና ቀኑን አትብሉም፥ አትጠጡም እኔና ደንገጥሮቼ ደግሞ እንዲሁ እንጾማለን(አስ 4፡16)
- የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ ለጾም አዋጅ ነገሩ፥ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ።(ዮናስ 3፡1-10)
- ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ አለም የመጣውና በስጋ የተገለጠው ለ2 ዐበይት ነገሮች ነው 1ኛ ራሱን መስዋእት አድርጎ እኛን ለማዳን ሲሆን 2ኛው ለእኛ ለክርስቲያኖች ማድረግ የሚገባንን ነገር ሊያሳየንና አርአያ ሊሆነን ነው፡፡ ስለዚህ እየሱስ ክርስቶስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊትም ከጦመ በኋላ ተራበ።(ማቴ 4፡1-5)
ከሀይል ሰጪ ምግብ የሚጾሙ
- በዚያም ወራት እኔ ዳንኤል ሦስት ሳምንት ሙሉ ሳዝን ነበርሁ።ማለፊያ እንጀራም አልበላሁም፥ ሥጋና ጠጅም በአፌ አልገባም፥ ሦስቱም ሳምንት እስኪፈጸም ድረስ ዘይት አልተቀባሁም።(ዳን 10፡2-3)
- ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ ሥጋዬም ቅቤ በማጣት ከሳ።(መዝ 108/109፡24)
ሌላው ጸሎትና ጾም አጋንንትን ማሸነፊያ እንደሆነ ጌታችን በ(ማቴ 17፡21) ተናግሯል፡፡
ሰባቱ(7) አጽዋማት
#1ኛ_ዐቢይ_ጾም(አርባ ጾም)
- ይህ ጾም በማቴ 4፡1 እና በሉቃ 4፡1 እንደተጻፈው ጌታ ራሱ የጾመው አርባ ጾም የሚባለው ነው፡፡ አርባ ጾም የተባለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ምንም ሳይቀምስ ለአርባ ቀንና አርባ ሌሊት ስለጾመው ስለጾመው እና ዲያብሎስን ድል እንዳረገው እኛም የሱን አርአያ በመከተል ነው የምንጾመው፡፡
#2ኛ_ጾመ_ሐዋርያት
- ከአብይ ጾም ቀጥሎ ሁለተኛው ጾም ጾመ ሐዋርያት(የሰኔ ጾም) ይባላል፡፡ ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ለስብከተ ወንጌል ከመሰማራታቸው በፊት የጾሙት ጾም ነው፡፡በዚህም የወንጌል ስራቸው ሰምሮላቸዋል፡፡ ስለዚህ አልጫ የነበረውን ዓለም በወንጌል ለማፋጠን ሐዋርያት ከጾም ከጸሎት ጋር የቱን ያህል እንደተጋደሉና መንፈስ ቅዱስም በሐዋርያት አድሮ የሰራውን ድንቅ ስራ ለማሰብ ነው፡፡
#3ኛ_ጾመ_ፍልሰታ
- ይህ ጾም ከነሐሴ 1 ቀን እስከ ነሐሴ 15 ቀን የሚጾም ነው፡፡ ይህ ጾም የእመቤታችን መታሰቢያ ነው፡፡ይህም እመቤታችን ከሞት ተነስታ በክብር ወደ ገነት ስታርግ ሐዋርያው ቶማስ ከተልዕኮ ሲመለስ ተገናኝተው የከፈኗን ጨርቅ ለበረከት ሰጥታዋለች፡፡ሐዋርያት ይሄንን ዜና ከቶማስ በሰሙ ጊዜ እነሱም የቶማስ ያየውን ያዩ ዘንድ አምላካችንን ከ ነሐሴ 1-15 ቀን በጾም ለምነውት ክርስቶስም ለጥያቄያቸው መልስ ሰጥቷቸዋል፡፡ስለዚህ ይህን ድንቅ ነገር ለማሰብና ይህን ጾም ምክንያት በማድረግ የተሰወረው መንፈሳዊ ሚስጢር ሁሉ በቸርነቱ ለቤተክርስቲያን የተገለጠ እንዲሆን በማለት ምእመናን በየአመቱ ጾመ ፍልሰታን ይጾማሉ፡፡
#4ኛ_ጾመ_ነብያት(የገና ጾም)
- ይህ ጾም ከሕዳር 15 እስከ ታህሳስ 28 ያለው ጊዜ ሲሆን በዓሉ(ልደት) በዘመነ ዮሐንስ ታህሳስ 28 ቀን ይውላል፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ከመገለጡና ሰው ከመሆኑ በፊት ነብያት የጌታን መምጣት በናፍቆት በጾምና በጸሎት ሲጠባበቁ ነበር፡፡ስለዚህ የነብያትን የጾም ድካም ለማሰብና አሁንም የአዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ደግሞ የሚመጣ ክርስቶስን በናፍቆት ሲጠባበቁ እንደ ነብያት መንፈሰ ኃይልን ለመልበስ በእምነት ለመጽናት ኃጢያትን ለመዋጋት ሲባል ይህን ጾም ክርስቲያኖች ይጾሙታል፡፡
#5ኛ_ገሃድ
ገሀድ ማለት ግልጥ የሆነ ለውጥ ማለት ነው፡፡ገሃድ የጥምቀት ብቻ ነው፡፡ ይኸውም ጥምቀት ረቡዕና ዓርብ ቀን በሚውልበት ጊዜ በኋላው የሚገኙ ማክሰኞና ሐሙስ የፍስክ ቀንነታቸው ወደ ጾምነት ተለውጦ ይጾማሉ፡፡ሆኖም ጥምቀት በሌላም ቀን ቢውል የዋዜማው ቀን ይጾማል፡፡
#6ኛ_ጾመ_ነነዌ
- የዚህ ጾም ጊዜ ሦስት(3) ቀን ብቻ ነው፡፡ቀኖቹም በየዓመቱ ሰኞ ማክሰኞና ረቡዕ ናቸው፡፡ የነነዌ ጾም በመባጃ ሐመር (አቆጣጠር) ከፍና ዝቅ ስለሚል አንድ ጊዜ በጥር አንድ ጊዜ በየካቲት ይሆናል፡፡የቤተ ክርስቲያን አባቶች ይህን ጾም የወሰኑት ልትጠፋ የነበረች ነነዌን በጾም ምክንያት እግዚአሔር ይቅር ስላላት ይህን አምላካዊ ይቅርታውን ለዘለዓለም ለማሰብና ዛሬም በዚህ ዓለም ከነነዌ የከፋ ርኩሰትና ኃጥያት ስላለ የነነዌን ሕዝብ ይቅር ያልክ አምካክ ዛሬም ይቅር በለን ለማለት ነው፡፡
#7ኛ_የረቡዕ_ዓርብ_ጾም
- ሰባተኛውና የመጨረሻው ጾም ረቡዕና ዓርብ ነው፡፡ አይሁድ ክርስቶስን በእንጨት ሰቅሎ ለመግደል የተፈራረሙበት ዕለት ረቡዕ ስለሆነ እና ዓርብ ደግሞ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ይህ ነው የማይባል መከራ የተቀበለበት የተሰቀለበትና የሞተበት እኛን ያዳነበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡
@EOTC_Wengel
23 views17:40