2022-08-26 06:42:31
ነሐሴ 20 ቀን፣ 2014
የንባብ ክፍል፡- ሆሴዕ 11፣ 12፣ 13 እና 14
ሆሴዕ 11፤ እስራኤል ግን አብዝቼ በጠራኋቸው ቁጥር አብዝተው ከእኔ ራቁ፤ አስተማራቸው፣ ፈወሳቸው፣ በፍቅር ሰንሰለት ሳባቸው፣ እነርሱ ግን ንስሓ መግባትን እምቢ አሉ፤ ዘወር ማለትን መረጡ፤ ኤፍሬም ሆይ፤ እንዴት እጥልሃለሁ? እስራኤል ሆይ፤ እንዴት አሳልፌ እሰጥሃለሁ? እግዚአብሔር ለእስራኤል ያለው ፍቅር!
ሆሴዕ 12፤ ኤፍሬም ሐሰትንና ዐመፅን ያበዛል፤ ተመለስ፤ ፍቅርንና ፍትሕን ጠብቅ፤ ዘወትር በአምላክህ ታመን፤ ነጋዴው ያጭበረብራል፤ መታበይ አለ፤ እግዚአብሔር ስለ ንቀቱ የሚገባውን ይከፍለዋል።
ሆሴዕ 13፤ ኀጢአት መሥራት አበዙ፤ ብራቸውን አቅልጠው ለራሳቸው ጣዖት ሠሩ፤ ከእኔ በቀር ሌላ አዳኝ የለም፤ ጠገቡ፤ ታበዩ፤ እግዚአብሔርን ረሱ፤ የእግዚአብሔር ቁጣ በእስራኤል ላይ ይገለጣል።
ሆሴዕ 14፤ እስራኤል ሆይ፤ በኀጢአትህ ምክንያት ስለ ወደቅህ ወደ አምላክህ ወደ እግዚአብሔር ተመለስ፤ ይቅር በለን፤ በምሕረትህ ተቀበለን በሉት፤ እግዚአብሔር እንደሚወዳቸውና ተሐድሶን እንደሚያደርግ ተናገረ፤ የምሰማህና የምጠነቀቅልህ እኔ ነኝ፤ የእግዚአብሔር መንገድ ቅን ነው፤ ጻድቃን ይሄዱበታል፤ ዐመፀኞች ግን ይሰናከሉበታል።
ከተማርኩት፡-
“እስራኤል ገና ሕፃን ሳለ ወደድሁት፤ ልጄንም ከግብፅ ጠራሁት። እስራኤል ግን አብዝቼ በጠራኋቸው ቁጥር አብዝተው ከእኔ ራቁ፤ … ኤፍሬምን እጁን ይዤ እንዲራመድ ያስተማርሁት እኔ ነበርሁ … በፍቅር ሰንሰለት ሳብኋቸው፤ … ዝቅ ብዬ መገብኋቸው።” እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያሳየው ፍቅር አስደናቂ ነው።
የሕዝቡ በደል፣ ዐመፅ በዝርዝር የቀረበበት መንገድ የሚገርም ነው። የሕዝቡ ዐመፅ እና የእግዚአብሔር ትዕግሥት፣ ፍቅር በንጽጽር ይታያል!
“ኤፍሬም ሆይ፤ እንዴት እጥልሃለሁ? እስራኤል ሆይ፤ እንዴትስ አሳልፌ እሰጥሃለሁ? … ልቤ በውስጤ ተናወጠ፤ ምሕረቴም ሁሉ ተነሣሥቶአል።”
“ስለዚህ ወደ አምላክህ ተመለስ፤ ፍቅርንና ፍትሕን ጠብቅ፤ ዘወትርም በአምላክህ ታመን።”
“እኔ ግን ከግብፅ ምድር ያወጣሁህ አምላክህ እግዚአብሔር ነኝ፤ ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አታውቅም፤ ከእኔም በቀር ሌላ አዳኝ የለም። በምድረ በዳ በሐሩር ምድርም ተንከባከብሁህ። ካበላኋቸው በኋላ ጠገቡ፤ በጠገቡ ጊዜ ታበዩ፤ ከዚያም ረሱኝ።”
“ከመቃብር ኀይል እታደጋቸዋለሁ፤ ከሞትም እቤዣቸዋለሁ፤ ሞት ሆይ፤ መቅሠፍትህ የት አለ? መቃብር ሆይ፤ ማጥፋትህ የት አለ? …”
ኀጢአታችንን ይቅር በለን፤ በምሕረትህ ተቀበለን ብላችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ የሚለው ጥሪ አስተማሪ ነው።
“… የምሰማህና የምጠነቀቅልህ እኔ ነኝ፤ … ፍሬያማነትህም ከእኔ የተነሣ ነው። ጥበበኛ የሆነ እነዚህን ነገሮች ያስተውላል፤ አስተዋይም እነዚህን ነገሮች ይረዳል።”
“የእግዚአብሔር መንገድ ቅን ነውና፤ ጻድቃን ይሄዱበታል፤ ዐመፀኖች ግን ይሰናከሉበታል።”
ቃሉን እንጸልይ፡-
ፍሬያማ የሚያደርገን እና የሚጠነቀቅልን የፍቅር አምላክ እግዚአብሔር ስሙ ይባረክ! ጸጋ ይብዛልን!
734 views03:42