Get Mystery Box with random crypto!

በደራ አማራዎች ላይ በአሸባሪ ኦነጋዊያን በተደጋጋሚ የሚፈጸምባቸው የግፍ እገታ፣ ግድያ፣ ዝርፊያ እ | አማራ ሚዲያ ማዕከል Amhara media center

በደራ አማራዎች ላይ በአሸባሪ ኦነጋዊያን በተደጋጋሚ የሚፈጸምባቸው የግፍ እገታ፣ ግድያ፣ ዝርፊያ እና ቃጠሎ በአስከፊነቱ ቀጥሏል፤ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ብቻ ከ100 በላይ ነዋሪዎች ታግተዋል።

አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ
መጋቢት 23 ቀን 2015 ዓ/ም
አዲስ አበባ ሸዋ

በሸዋ የደራ አማራዎች በአሸባሪ ኦነጋዊያን በተደጋጋሚ የሚፈጸመው የግፍ እገታ፣ ግድያ፣ዝርፊያ እና የቤቶች ቃጠሎ ዛሬም በአስከፊነቱ ስለመቀጠሉ ለአማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ከስፍራው እየደረሱ ያሉ መረጃዎች አመልክተዋል።

ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በቡድኑ ታግተው ወደ ጫካ ከተወሰዱት ከ100 በላይ ሰዎች መካከል በርካቶች ገንዘብ ከፍለው ሲለቀቁ የተገደሉ እና ደብዛቸው የጠፉ፣ መኖሪያ ቤታቸው የተቃጠለባቸው ወገኖች ስለመኖራቸው ለማወቅ ተችሏል።

ይህ ሲሆን የኦህዴድ ብልጽግና የክልሉ አገዛዝም ሆነ የፌደራል ፖሊስ አማራዊ የማንነት ጥያቄው ለዘመናት ታፍኖ ሲሳደድ ለኖረው ህዝብ እየደረሱ እንዳልሆነ ተገልጧል።

ከመንግስት አካላት ጭምር ስንቅ፣ ትጥቅ እና መረጃ የሚያገኙ በተለያዩ ጊዜያት ከኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች ከ30 በላይ ባንኮችን የዘረፉ ራሳቸውን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ነን የሚሉ አሸባሪ ኦነጋዊያን በደራ አማራዎች ላይ የሚፈጽሙት ሁለንተናዊ ግፍ ማቆሚያ አለማግኘቱን ተከትሎ ከ2 ወራት በፊት ሚሊሾች ከአካባቢው መስተዳድር ጋር በመተባበር የተያዙ ከ7 በላይ ቀበሌዎችን ነጻ አውጥተዋቸው እንደነበር ተሰምቷል።

ይህ ተጋድሎ ከተደረገ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ አንዳንድ የደራ ወረዳ አመራሮች የአማራ ሚሊሾችን ፋኖ ናቸው በማለት ለማስመታት እና ለማሳፈን ሙከራ በማድረጋቸው ግንኙነቱ እየላላ በመምጣቱ አሁን ላይ የሽብር ቡድኑ አባላት ወደለቀቋቸው ቀበሌዎች ጭምር ሰርገው እየገቡ ንጹሃንን አግተው እየወሰዱ፣ እየገደሉ እና በመቶ ሽህ የሚቆጠር ገንዘብ እያስከፈሉ መሆናቸው ተነግሯል።

ባሳለፍነው ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ከ100 በላይ ነዋሪዎች የታገቱ ሲሆን በያዝነው መጋቢት ወር ብቻ በደራ ወረዳ የተለያዩ ቀበሌዎች 75 ሰዎች በአሸባሪ ቡድኑ ታግተው ወደ ጫካ ተወስደዋል ብለዋል ነዋሪዎቹ።

ይኸውም:_

1) ከሀርቡ ደሶ ቀበሌ:_
15 ሰዎችን አግተው በመውሰድ እስከ 200 ሽህ ብር እንዲከፍሉ እየተደረገ ነው።

2) በመንቃታ ቀበሌ:_
30 ሰዎችን አግተው ወስደዋል።

21 የሚሆኑት 200 ሽህ ብር ከፍለው ተለቀዋል።

3) ማካፍታ ጅሩ ሮጌ:_
በመጋቢት 3ተኛ ሳምንት 5 ሰዎችን አግተው ወስደዋል።

ታፍነው የተወሰዱት ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ አልተመለሱም።

4) ከሩሱባ ቀበሌ:_
6 ሰዎችን ታፍነው ተወስደው አልተመለሱም።

5) በቾ ቀበሌ:_
2 ሰዎች ታፍነው ተወስደው አልተመለሱም።

6) አዳሃ መልኬ ቀበሌ:_
10 ሰዎች ታፍነው ወደ ጫካ ተወስደዋል።

7) ወሬ ገብሮ:_
7 ሰዎች ታግተው በቡድኑ ተወስደዋል።

ከታገቱት መካከልም አማራዎችን እየለዩ በመግደል እና አፍኖ ደብዛ በማጥፋት ላይ ስለመጠመዳቸው ከነዋሪዎች ለአሚማ የደረሰው መረጃ አመልክቷል።

አግተው የወሰዷቸውን ለማስለቀቅ ሚሊሾች ወደ አካባቢው እንዳይሄዱም ሆንተብሎ በሀሰት የአማራን ስም በመጥራት እያጠፉ በመሆን አስቸጋሪ መሆኑ ተገልጧል።

የፌደራል ፖሊስ በቱቲ የሚኖሩ የአማራ ሚሊሻዎችን አብረን እንዝመት በማለት ከዘመቱ በኋላ በክህደት የደራ አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊን አቶ አሰፋ ነበበን ለማፈን ሙከራ ማድረጉ እና ከተወሰነ ጊዜ በኋላ እንዲፈታ መደረጉ ይታወሳል።