Get Mystery Box with random crypto!

ዘካቱል ፊጥር ዘካተል ፊጥር የረመዳን ወር ፆም መጠናቀቅ ተከትሎ በወቅቱ ሙስሊም ሁኖ በህይወት | አፍሪካ ቲቪ | Africa TV1

ዘካቱል ፊጥር

ዘካተል ፊጥር የረመዳን ወር ፆም መጠናቀቅ ተከትሎ በወቅቱ ሙስሊም ሁኖ በህይወት ባለ ሰው በነፍስ ወከፍ ግዴታ የሚሆን የዘካ / ሰደቃ/ አይነት ነው ፡፡ ለግንዛቤ ያህል ዘካተል ፊጥር ከዘካተል ማል ይለያል ።

እያንዳንዱ አባወራ ወይም እማወራ ወይም አስተዳዳሪ የራሱን ጨምሮ በእርሱ ስር እየቀለባቸው ላሉ ቤተሰቦቹ ሁሉ መስጠት ይኖርበታል ፡፡

አብዱላህ ኢብን አባስ አላህ ይውደዳቸውና እንዲህ ይላሉ፤
‹‹የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም
በ እርሳቸው ላይ ይሁን) ዘካተል ፊጥር ለፆመኛ በጾሙ ወቅት ከፈፀማቸው ጥቅም አልባ ውድቅ ንግግሮችና ተግባሮች ጥፋት እንዲሁም የተቃራኒ ፆታ ስሜትን ቀስቃሽ ለሆኑ ንግግሮቹ ጥፋት ማፅጃ ይሆንለታል ። ለሚስኪኖች (ድሆች) መብል ሲሆን በግዴታ መልኩ ደንግገውላታል ። ስለዚህም ከኢድ ሰላት በፊት (ዘካውን በመስጠት ግዴታውን የተወጣ) ተቀባይነት ያለው ዘካን ሰጥቷል፤ ከ ኢድ ሶላት ቦሃላ ዘካውን የሰጠ እንደማንኛውም ሰደቃ አንዱ እንደሆነ ይታሰብለታል ።))
(አቡዳውድ እና ኢብኑ ማጃህ ዘግበውታል)።

ኢብኑ ሙንዚር አል ኢጅማዕ’ በተሰኘው ኪታባቸው ‹‹ዒልምን የተማርንባቸው
ዑለሞች ሁሉ ዘካተል ፊጥር ግዴታ መሆኑን
ተስማምተውበታል›› በማለት የ ኡለሞችን አጠቃላይ ስምምነት (ኢጅማዕ) የተገኘበት መሆኑን ጠቁመዎል ።

:-የተደነገገበት ጥበብ

ከላይ ግዴታነቱን ለማመላከት በተጠቀሰው ሀዲስ እንደተጠቀሰው ፣ ድሆች በባዕሉ (ዒድ) እለት ሰዎችን ከመለመን እንዲድኑና የእለቱ ደስታ ተካፋይ እንዲሆኑ ማድረግ እንዲሁም በፆም ወቅት ተከስተው ላለፉ አንዳንድ ጉድለቶች (ግድፈቶች) ማሟያ እንዲሆን ነው ።

:-መጠኑ

* የዘካተል ፊጥር መጠን ኢብኑ ኡመር ረዲየላሁ አንሁ ከነብያችን ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም ይዘው ባስተላለፉት ሀዲስ እንዲህ ብለዋል: – ‹‹የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በሳቸው ላይ ይሁን) ከተምር ወይም ከገብስ አንድ ቁና መስጠት በ እያንዳንዱ ሙስሊም፤ ባሪያም ሆነ ጨዋ (ባሪያ ያልሆነ)፣ሴት፣ ህፃን፣ አዋቂ ላይ ግዴታ አድርገዋል፡፡ እንዲሁም ሰዎች ወደ (ዒድ) ሰላት ከመውጣታቸው በፊት ለሚገባቸው ሰዎች እንዲደርስ አዘዋል፡፡›› (ቡኻሪና ሙስሊም )

1 ሷዕ / ቁና/ በመካከለኛ ሰው እጅ አራት እፍኞች ነው ። ወደ ኪሎ ግራም ሲቀየር እንደየ እህሉ ክብደትና ቅለት ይለያያል ። ለምሳሌ ፣
— አንድ ቁና (ሳእ) ፉርኖ ዱቄት 2.5 ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) ጤፍ 2·85 ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) ሩዝ 2·75 ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) ስንዴ 2·5 ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) ገብስ 2 ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) ማሽላ 2·63ኪሎ
— አንድ ቁና (ሳእ) በቆሎ 2·5 ኪሎ

:-ግዴታ የሚሆነው በማን ላይ ነው

— ሙስሊም በሆነ
— ረመዷን ወር ሲጠናቀቅ በህይወት የነበረ
— በእለቱ ለ24 ሰዓት ለራሱና ለሚያስተዳድራቸው ሰዎች ወጪ የሚያደርገው ሀብት ኑሮት ከዚያ የተረፈ ባለው ሰው ።

— * ዘካተል ፊጥር በነፍስ ወከፍ የሚደረግ ኢባዳ ስለሆነ በቤተሰብ ስር የሚኖር ሰው ለራሱ ሚያወጣበት ነገር ካለው ቤተሰቦቹን ከመጠበቅ ራሱ ማውጣት ይኖርበታል ።

የሚሰጥበት/የሚወጣበት ጊዜ

* ዘካተል ፊጥርን ማውጣት ግዴታ የሚሆነው የረመዷን ወር የመጨረሻው እለት
ፀሀይ ከጠለቀችበት ወይም ዒድ መሆኑ ከተረጋገጠበት ሰዓት አንስቶ የኢድ ሷላት ተሰግዶ እስኪጠናቀቅ ድረስ ነው ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢብኑ ዑመርን ጨምሮ ሌሎቹም ሰሀቦች (ረዲየላሁ አንሁም) ከዒድ አንድ ወይም ሁለት ቀን ቀድሞ ዘካተል ፊጥርን ማውጣት እንደሚቻል ይገልጻሉ ሲተገብሩትም ነበር ።

* ዘካተል ፊጥርን ከ(ዒድ) ሰላት በኋላ ማዘግየት የተከለከለ ነው ። ድንገት አንድ ሰው ረስቶ ወይም ሳይመቸው ቀርቶ በወቅቱ ሳያወጣ ቢቀር ባስታወሰና በተመቸው ወቅት ማውጣት አለበት ።

:- የሚሰጠው ነገር
* ለዘካተል ፊጥር የሚሰጡ የእህል አይነቶችን በተመለከተ አውጪዎቹ በሀገራቸው ከሚመገቡዋቸው እህሎች ውስጥ ይሆናል ለምሳሌ እንደ ተምር ፣ ዱቄት ፣ እሩዝ ፣ በቆሎ፤ ጤፍ …. ወዘተ ባሉ የምግብ እህል አይነቶች
ነው ። ይህን አስመልክተው የአላህ መልእተኛው ነብያችን (የአላህ ሰላትና ሰላም በሳቸው ላይ ይሁን) በሀዲሳቸው የጠቀሷቸው የምግብ እህሎች ( ገብስ፤ ተምር፤ ዘቢብ) ፣ የመሳሰሉት ሲሆኑ፣ ነገር ግን የምግብ አይነቶቹ በነዚህ ላይ ብቻ እንደማይገደቡ የኢስላም ሊቃውንቶች ያስረዳሉ ። በዚህም መሰረት በማንኛውም አካባቢ የሚኖር ሙስሊም ማህበረሰቡ አዘውትሮ ከሚመገባቸው የምግብ እህሎች ዘካተል ፊጥሩን ማውጣት ይችላል፡፡

?:-ለማን ይሰጥ

* ዘካተል ፊጥር ለምስኪኖች እና ለድሆች ብቻ ነው ሚሰጠው አብደላህ ብኑ አባስ ባስተላለፉት ሀዲስ ላይ ነብያችን (የአላህ ሰላትና ሰላም በሳቸው ላይ ይሁን) ‹‹ለምስኪኖች መብል …›› በማለት ስለገለፁ ።

በዘካተል ፊጥር ስለመወከል

* ዘካተል ፊጥር የሚሰጥበት ወቅት የተገደበና ግዜውም አጭር ከመሆኑ አንፃር አውጪዎች ባሉበት ሀገር ወይም ሁኔታ ምክንያት በተወሰነለት ግዜ ማውጣት ካልቻሉ ወቅቱ ሳያልቅ ዘካውን ሚያወጣላቸው ሰው መወከል ይችላሉ ። በተመሳሳይ ዘካተል ፊጥርን የሚቀበሉ ምስኪኖችም ራሳቸው መቀበል ካልቻሉ ሚቀበልላቸውን ሰው መወከል ይችላሉ ።