2022-09-01 10:38:53
የገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን 3 መጻሕፍት ሰኞ ይመረቃሉ
*ዛሬ ከሰዓት በኋላ ስለምርቃቱ መግለጫ ይሰጣል
የተወዳጇ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የሆነው አንጋፋው ደራሲ፣ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን ሦስት መጻሕፍት የፊታችን ሰኞ ይመረቃሉ፡፡
መጻሕፍቶቹም፡- ነገም ሌላ ቀን ነው፣ የመጨረሻው ንግግር እና የእኛ ሰው በአሜሪካ የተሰኙት ሲሆኑ ፤ ታላላቅ የኪነጥበብ ባለሞያዎች ሥራዎቻቸውን በሚያቀርቡበት መድረክ ነው የምርቃት ሥነሥርዓቱ የሚከናወነው ተብሏል፡፡
ሰኞ ነሐሴ 30 ቀን 2014 ዓ.ም ቦሌ በሚገኘው ፍሬንድሺፕ ኢንተርናሽናል ሆቴል በሚዘጋጀው ልዩ የምረቃ ሥነሥርዓት ላይ አንጋፋዎቹ አርቲስት አበበ ባልቻ ፣ አርቲስት ተፈሪ አለሙ ፣ ወግ አዋቂው በሃይሉ ገብረመድህን ፣ አርቲስት ጌትነት እንየውን ጨምሮ ሌሎችም የኪነጥበብ ባለሞያዎች ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሏል።
የምረቃ ሥነሥርዓቱ መደበኛ የመግቢያ ዋጋ 300 ብር ሲሆን ከነጻ ኮክቴል እራት ጋር ለVlP 1000 ብር መሆኑ ታውቋል፡፡
በዕለቱ ከሚመረቁት መጻህፍት መካከል አንዱ የሆነው ነገም ሌላ ቀን ነው፣ ዝነኛው የአሜሪካ ክላሲክ መጻሐፍ Gone With The Wind ትርጉም ሁለተኛ ክፍል መጽሐፍ ሲሆን ገጣሚ ነቢይ መኮንን በደርግ ዘመን በእስር ላይ እንዳለ በሲጋራ መጠቅለያ ወረቀቶች ላይ በድብቅ የተረጎመው እንደሆነ ይታወቃል፡፡
መጽሐፍቶቹን በጠይም መጻሕፍት /አራት ኪሎ ቅድስት ሥላሴ ሕንፃ አንደኛ ፎቅ /ላይ ማግኘት ይቻላል ተብሏል፡፡
የምረቃ ሥነሥርዓቱን አስመልክቶ ገጣሚ ነቢይ መኮንንና የፕሮግራሙ አዘጋጆች ዛሬ ከሰዓት በኋላ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከ20 ዓመታት በላይ የዘለቀችውን ሳምንታዊ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ከመሰረቱት አንዱ የሆነውና አሁንም በዋና አዘጋጅነት እየሰራ የሚገኘው ነቢይ መኮንን፣ ከዚህ ቀደም ሁለት የግጥም መድበሎችን ያሳተመ ሲሆን ናትናኤል ጠቢቡ የተሰኘውን ጨምሮ ሌሎች ተውኔቶችንም ለመድረክ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡
826 views07:38