Get Mystery Box with random crypto!

ምናለ_ባይነጋ @ሀይማኖት_ንጉሴ (የዲማው) ይኼው ደሞ ነጋ፥ በስተ-ምስራቅ ወጣች፥የዘልማድ ፀሐይ | ግጥም በማሙሽ እና ሀይማኖት

ምናለ_ባይነጋ

@ሀይማኖት_ንጉሴ (የዲማው)

ይኼው ደሞ ነጋ፥
በስተ-ምስራቅ ወጣች፥የዘልማድ ፀሐይ፣
ለፍጡራን ሁሉ፥
ተስፋ ልትፈነጥቅ፥
ጨለማን ልትገልጥ፥ብርሃን ልታሳይ፣

ታዲያ ምነው ለ'ኔ፥
ህመም ይዛ መጣች፥ከፍጡር ለይታ፣
ታንቺ ልብ ጋራ፥
አጥብቄ ያሰርኹትን፥
የፍቅር ሰንሰለት፥በጣጥሳ ልትፈታ፣

ይሻለኛል እኔ፥
ጭጋግ የወረሰው፥
ፅልመት የከበበው፥የሰማይ ማኩረፉ፣
ምን አለኝ ተቀኑ፥
ምን አለኝ ተንጋት፥
ደስታን ከሚሰጠኝ፥
ከትዝታሽ ጋራ፥መነጠል ነው ትርፉ፣

ሌሊቱ ምን ነስቶኝ፥
በጉጉት ናፍቄ ፥ምጠብቅ ጀምበሯን፣
መች አነሰኝ ለ'ኔ፥
አንቺን ለማስታወስ፥
አትነጠቅ እንጂ፥ጨረቃ ማማሯን፣

ታስታውሰኛለች፥
ከጥቁሩ ሰማይ ላይ፥
ውበትሽን አያለሁ፥በጨረቃ በኩል፣
ነጫጭ ከዋክብትን፥
ታንቺ እያወዳደርኩ፥
አቻ እፈልጋለሁ፥ከጥርሶችሽ እኩል፣
እንዲህ ነው ማነጋው፥
ቁስሌን እያባበልኩ፥
የተከዳው ልቤን፥በትዝታሽ ስኩል፣

ነፋሱ ጠረንሽን፥
ጨረቃ መልክሽን፥
ሰማዩ ምስልሽን፥
አጉልቶ እየሳለ፥
ወደ'ኔ ሲያመጣሽ፥አልለውም በቃኝ፣
ትዝታሽ ነው'ና፥
ታሸለበኝ እንቅልፍ፥
ተብቸኝነቴ፥ቀስቅሶ 'ሚያነቃኝ፣

ታዲያ ለምን ብዬ፥
ታንቺ ሚወስደኝን፥ጨለማውን ልርገም፣
ላመስግነው እንጂ፥
እድሜው እንዲበዛ፥ፀሎት መ'ፃፍ ልድገም፣

መጥላትስ ንጋትን፥
መርገምስ ንጋትን፥
በቁስሌ ሽንቁር ስር፥ሻጣ እየሰደደ፣
ሰርክ እያሳመመኝ፥
ብቻዬን ሳወራ፥
በሀሜተኞች አፍ፥ያስባለኝ አበደ፣

መራገምስ ቀኑን፥
አንቺን ላያስረሳኝ፥
ከህይወት ማህደር፥
ክህደትሽን ብቻ፥ፊቴ እየጋረጠ፣
ሌቱ የቸረኝን፥ደስታ እያቋረጠ፣

ስጋን ለሚቦጭቅ፥
ለሀሜታም ምላስ፥ሰ'ቶኝ አሳልፎ፣
ንጋት አይደለም ወይ፥
አበደ ያስባለኝ፥
ውሸታም መስካሪ፥ሰብስቦ አሰልፎ፣

ይህንን እየፃፍኩ፥
የብርሃን ፍላፃ ካ'ይኔ ተተከለ፥
ክፍቱን በረሳሁት፥በመስኮቴ ታየኝ፣
የዘልማድ ፀሐይ፥
በስተምስራቅ ወጣች፥
ከትዝታሽ ጋራ፥ታ'ንቺ ልትለየኝ፣

ጀምበር ዐይኗ ይጥፋ፥
በምዕራብ ስትጠልቅ፥ምስራቅ በሩን ይዝጋ፣
አሁን ምን ቸገረው?፥
ታ'ንቺ ባይነጥለኝ፥ሌሊቱ ባይነጋ።